IRROB.ORG

Home » Miscellaneous » News Releases » Abba Teum Tesfay’s Biography

Abba Teum Tesfay’s Biography

abba-teum-tesfay1ዜና ዕረፍት
በየካቲት 2: 2006  ዓ.ም.  በትግራይ ክልል በምብራቃዊ ዞን በኢሮብ ወረዳ በልደታ ማርያም ካቶሊክ ቤተ ክርስትያን ስርዓተ ቀብራቸው የተፈጸመ ነፍሰ ኄር ኣባ ጥዑም ተስፋይ ከወላጆቻቸው ኣቶ ተስፋይ ደበሳይና ከእናታቸው ወ/ሮ ባህጉ ወልደ በኢሮብ ወረዳ ልዩ ስሙ ዳውሃን በተባለችው መንደር በታህሳስ 17: 1947  ዓ.ም. ተወለዱ::

ነፍሰ ኄር ኣባ ጥዑም ተስፋይ  ኣንደኛ ደረጃ ትምህርታቸው  ከ1960 – 1965 ዓ.ም. በልደታ ለማርያም ተከታትለዋል::  በ1966 ዓ.ም. የሰባተኛ ክፍል ትምህርታቸው  በሲታውያን ገዳማዊያን ማህበር በመግባት በአሥመራ ተከታትለዋል:: ከ1968 -1969 ዓ.ም. በመንዲዳ በሲታዊያን ማህበር 8ኛና 9ኛ ክፍል ተምረዋል:: በ1970 ዓ.ም. በማህበሩ ሕጊ መሰረት በመንዲዳ የአንድ ዓመት አገልግሎት ፈጽሟል:: በ1971 ዓ.ም 10ኛ ክፍል በአድስ አበባ ከተድራል 2ኛ ትምህርት ቤት ካጠናቀቁ በኋላ 11ኛ ና 12ኛ  ክፍል ከ1972-1973 ዓ.ም. በአድስ አበባ ዘርአ ክህነት አጠናቅቀዋል:: ከ1974 – 1976 ዓ.ም.  በኣሥመራ በአቡነ ሰላማ ከሳቴ ብርሃን ታዕካ ጥበብ ቶሎጊያና ፍልስፍና ተቋም የሁለት ዓመት ፍልስፍናና የአንድ ዓመት ትምህርተ መለኮት ተምሯል:: ከ1977 -1979 ዓ.ም. በአድግራት ከፍተኛ መንፈሳዊ ኮለጅ ለሶስት ዓመት የትምህርተ መለኮት ትምህርት ከተከታተሉ በኋላ በሚያዝያ 18: 1979 ዓ.ም. ከሶስት የትምህርት ጓደኞች ጋር መዓርገ ክህነት በብጹዕ አቡነ ኪደነማርያም ተክለኃይማኖት እጅ ተቀብለዋል::

ነፍሰ ኄር ክቡር አባ ጥዑም ተስፋይ መዓርገ ክህነት እንደ ተቀበሉ  በዓሊቴና የልደታ ማርያም ቆሞስ ተሰይመው ከ1980 -1989 ዓ.ም. ከፍተኛ መንፈሳዊ አገልግሎት አበርክተዋል::

በ1990 ዓ.ም. ለከፍተኛ ትምህርት ወደ ሮማ ተላኩ:: ከ1990 -1994 ዓ.ም. በዮሃንስ ላተራን ጳጳሳዊ ዩንቨርስቲ ፓስቶራል ትዮሎጂ አጥንተው በማስትረይት ድግሪ ተመርቀዋል:: ትምህርታቸው በብቃት ከፈጸሙ በኋላ ወደ ትውልድ አገራቸው ተመልሰው በአድግራት ሃገረ ስብከት የምእመናንና የወጣቶች መሪ ካህን በመሆን  ከ1995 -2000 ዓ.ም. እያገለገሉ ቆይተዋል::  ቀጥሎም  የአመራር ብቃታቸው ታይቶ በአድግራት ሃገረ ስብከት ካቶሊክ ጽህፈት ቤት ምክትል አስተዳደሪና የሃዋርያዊ ስራ መሪ ሆነው እስከ እለተ ህልፈታቸው ጥር 30: 2006 ዓ.ም. ክህነታዊ አገልግሎታቸው በብቃትና በታታሪነት እየተዋጡ ቆይቶዋል:: በስራ ዘመናቸው  በኢትዮያና በዩጋንዳ ከሃለፍነታቸው ጋር የሚሄድ በርከት ይሉ ስልጠናዎች እንደ ወሰዱ የግል ማህደራቸው ያመለክታል ::

ነፍሰ ኄር ኣባ ጥዑም ተስፋይ ከመደበኛ ስራቸው በሻገር የአገር አቀፍ የአብያተ እምነቶች ተቋማት ጥምረት የብሄራዊ ኮሚቴ አባል በመሆንና በትግራይ ክልል የአብያተ እምነቶች  ጥምረት ኮሚቴ አባል በመሆን  በኀብረተ ሰብ መካከል ለላም ለማስፈን ጥረት እያደረጉ የቆዩ ታታሪ ካህን እንደነበሩ የስራ ባልደረቦቻቸው የሚመሰክሩላቸው ሀቅ ነው:: ከዚህ በተጨማሪም  “ ፍትህና ሰላም በኅብረተሰብ ውስጥ ማስፈን” ከምለው የካቶሊክ ቤተ ክርስትያን መርሆ በመነሳት የአድግራት ሀገረ ስብከት በመወከል ከኦርቶድክስ ቤተ ክርስትያን፣ከእስልምና ሃይማኖት፣ ከህብረተሰብ የተመረጡ የእድሜ ባለፀጋዎችና  ከመንግስት መዋቅር የተወከሉት የህግ ባለሟዎች ኮሚቴ በለቀመንበርነት በመምራት በርከት ያሉ የእርቅ ስነ ስርዓቶች በመፈጸም ኅብረተሰቡ ከግጭትና ህውከት ተላቆ ሰላማዊ ህወታቸው እንድመሩ ያደረጉ ታላቅ የሰላም ሃዋርያ እንደነበሩ ባለፉት ሶስት ዓመታት ባሳዩት የስራ እንቅስቃሴያቸው አስመስክረዋል::

ሳሆ፣ ትግርኛ፣አማርኛ፣እንግልዝኛና ጣሊያንኛ ቋንቋዎች ችሎታ የነበራቸው ነፍሰ ኄር ኣባ ጥዑም ተስፋይ ለፍትህና ሰላም ልዩ ትኵረት የነበራቸው ፤ ሰው አክባሪ፣ትሁት፣ቅኑ ፣ፈገግታ ከፊታቸው የማይለያቸው ፍቅር ሰጥቶ ፍቅር የመቀበል ችሎታ የነበራቸው በቤተክርስትያንና በኅብረተሰብ እጅግ ተወዳጅና ባለመልካም ባህሪ ካህን ነበሩ::

እኝህ ታታሪና አመለ-ወርቅ ካህን ያጣችው ቤተ ክርስትያን፣ ቤተሰብ፣ጓደኞችና ኅብረተሰብ ፅናት እየተመኘን  ለነፍሰ ኄር ኣባ ጥዑም ተስፋይ እግዚአብሔር በዘለዓለማዊ መንግስቱ እንድያሳርፍልን እንጸልያለን:: 

ካቶሊክ ቤተ ጳጳስ ዘመንበረ አዲግራት 

02. 06.2006 ዓ.ም.

Weight Loss

%d bloggers like this: